“ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትራችን ከሶስት ቀናት በፊት ያስጀመሩትን የክረምት በጎ ፈቃድ ስራ ተከትሎ እኛም ዛሬ 3500 የሚሆኑ የመኖሪያ ቤት ዕድሳት አስጀምረናል።
ልበ–ቀና ባለሀብቶችንና ሕዝባችንን በማስተባበር የበርካታ ነዋሪዎቻችንን ችግር መቅረፍ የሚያስችል የቤት እድሳት መርሀ–ግብራችንን የጀመርነው በልደታ ክፍለ ከተማ በተለምዶ ቆርቆሮ ሰፈር ተብሎ በሚጠራው ከ18 ዓመታት በላይ በቆርቆሮ ቤት ውስጥ የሚኖሩ 134 አባወራዎችን እና በአራዳ ክፍለ ከተማ ራስ መኮንን ድልድይ አካባቢ የሚኖሩ 15 አባወራዎችን መኖሪያ ቤት ዕድሳት በማስጀምር ነው፡፡
የከተማችንን ገጽታ የሚቀይር ታላላቅ ፕሮጀክቶችን ከመገንባት ጎን ለጎን በሰው ተኮር ስራዎቻችን የሀገር ባለውለታዎችንና አቅመ ደካማ ነዋሪዎችን ከከተማዋ ዕድገት ፍትሐዊ ተጠቃሚ እንዲሆኑ በትጋት መስራታችንን እንቀጥላለን።“
በጎ ፍቃደኝነት ለህሊና እርካታ፤ ለሀገር እድገት !!
በከተማችን አዲስ አበባ የህዝባችን የኑሮ ጫና ለማቃለልና መሰረታዊ በሆነ መልኩ ኑሮውን ለማሻሻል አበረታች ጥረቶች እየተደረጉ ይገኛሉ። ለአብነትም የምገባ ፕሮግራም፣ በዝቅተኛ የኑሮ ደረጃ ለሚገኙ ዜጎች የቤት ግንባታ እና እድሳት፣ የእሁድ ገበያና የመሰረታዊ ሸቀጦች አቅርቦት የመሰሳሰሉ ጥረቶችን መጥቀስ ይቻላል።
የህዝባችንን የኑሮ ዘይቤ ለማሻሻል በተዘረጉ የከተማ ግብርና እና የሌማት ቱሩፋት ፕሮግራሞች በውስን ቦታዎች ላይ የቤተሰብን ፍላጎት አሟልቶ ለገበያ ጭምር የሚተርፍ ምርት ማግኘት እንደሚቻል ፈጥነው ተግባራዊ ካደረጉት ስኬታማ ግለሰቦች ተሞክሮዎች እየሰፉ ነው።
በየደረጃው የሚገኘው አመራራችን በመደበኛነት የህዝቡን ልማት እና አስተማማች ሰላሙን ከማረጋገጥ ባሻገር በጎ ፍቃደኝነት የህሊና እርካታ የሚሰጥ መሆኑን በመረዳትና ለሀገር ወሳኝ መሆኑን በማመን በጎ ግለሰቦችንና ተቋማትን በማስተባበር እንዲሁም የአገልግሎት አሰጣጥና የመልካም አስተዳደር ችግሮችን ለመፍታት ከሚያደርገው ጥረት ባሻገር የ60 እና የ90 ቀናት ዕቅድ ነድፎ ሁሉንም አቅሞች አስተባብሮ ሌት ተቀን እየተጋ ይገኛል።
የሀገራችንም ይሁን የከተማችን ብልፅግና እውን የሚሆነው በእያንዳንዳችን ላብ ነው። ከስራ እና ከስራ ውጭ አማራጭ የብልፅግና መንገድ የለምና ጉልበታችን፣ እውቀታችንና ገንዘባችንን አቀናጅተን እና ተቀናጅተን በመስራት ሽርፍራፊ ሰከንድ ሳናባክን ጊዜአችንን እራሳችንን፣ ቤተሰባችንን እንዲሁም ሀገራችንን ለመለወጥና ለማበልፀግ ልንጠቀምበት ይገባል።